ስነ-ህዝብና የተባባሰው ሰብዓዊ ቀውስ
ሐሙስ፣ ኅዳር 30 2008
„The State of Population 2015“ የሚል ርዕስ የተሰጠውና ዛሬ በአዲስ አበባ ይፋ የተደረገው የUNFP ዘገባ በተፈጥሯዊ አደጋዎች ምክንያት ለድህነት ይጋለጣሉ ከተባሉ 11 ሃገሮች መሃል ኢትዮጵያ አንዷ መሆኗን አስታውቋል ። ዘገባው ኢትዮጵያን ጨምሮ ኒጀር፣ ማሊ፣ ሶማሊያ፣ ቡሩንዲ እና ቻድ በሃይለኛ ድርቅ ሊጎዱ የሚችሉ አገሮች ናቸዉ ሲል ያብራራል።ከአፍሪቃ ቀንድ በጎርጎሮሳዊው በ2014 በግጭት እና ሁከት ምክንያት በአገር ዉስጥ ከቤት ንብረቱ የተፈናቀለ ህዝብ በሶማሊያ ከ1,1 ሚሊዮን በላይ ሲሆን በኢትዮጵያ በ397,200 በኤርትራ ደግሞ 10,000 ይደርሳል ተብሏል። ከአፍሪቃ አገሮች ኢትዮጵያ በርካታ ስድተኞችን እንደምታስተናግድ የሚናገሩት በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስነ-ሕዝብ ፈንድ ዋና ዳይሬክተር ፋዉስትን ያሆ አብዛኛዎቹ ስደተኞች ከ ደቡብ ሱዳን እንደሚመጡ ይናገራሉ።
"በደቡብ ሱዳን ለስደት ዋነኛዉ ምክንያት በእርግጥ ጦርነት ነዉ። የሚያሳዝነዉ ሌሎች የአፍሪቃ አገሮችም የሰብዓዊ ቀዉስን ተከትሎ ከአንድ ቦታ ወደ አንድ ቦታ የሚንቀሳቀሱት በጦርነት እና በትጥቅ ትግል ሰበብ ነዉ።ሰዎችን ከቄያቸዉ ገፍቶ የምያወጣቸዉ ሁለተኛዉ ምክንያት ደግሞ በአሁኑ ግዜ በአፍሪቃ ቀንድ እያየነዉ ያለነዉ ከድርቅ ጋር የተገናኘ ሰብዓዊ ቀዉስ ነዉ። በአሁኑ ሰዓት እኛን የሚያሳስበን ሌላ ከባድ ሰብዓዊ ቀዉስ በኢትዮጵያና ለሎች በአፍሪቃ ቀንድ በሚገኙ ሀገሮች ይከሰታል ብለን ነዉ።"
ጥናቱ ዛሬ በዓለማችን ከሚደርሰው የእናቶች ሞት ፣ሶስት አምስተኛዉ በስደቶኞች መጠለያ እንደሚከሰት ጠቅሶ በየቀኑ 507 ሴቶች እና ወጣት ልጃገረዶች በእርግዝና ወቅት በሚፈጠሩ ውስብስብ ችግሮች እና፣ በድንገተኛ ወሊድ ወቅት ለሞት እንደሚዳረጉ አትቷል። ለስነ-ተዋልዶ አስፈላጊ የሆኑ የመሰረተ-ልማቶች እጦት ከወሊድ ጋር ተያይዞ የሚመጣውን ችግር እንዳባባሰው ፋዉስትን ያሆ ይናገራሉ።
"ስደተኞች ከቦታ ቦታ ሲንቀሳቀሱ እና እነሱን የሚቀበል አገር ሲያገኙ ግን የሚቀበላቸዉ አገር በጤና ጥበቃ የተካነና የጤና አግልግሎቶችን የሚሰጥ ከሆነ በእቃ አቅርቦትና በጤና ስርዓቱ ዉስጥ ስደተኞቹን ተጠቃሚ እንዲሆኑ ያስችላቸዋል። ግን እንደ አለመታደል ሆኖ ይህን ማቅረብ የማይችል ማኅበረብ ዉስጥ ነዉ ያለነዉ። ያ ማለት በጤና ጥበቃ መርኅ አኳያ በደንብ የየተካኑ አይደሉም። የተፈጠረዉን ቀዉስ ተከትሎ ርዳታ ቢገኝም ግን በጣም በቂ አይደለም። ወደ 700 ሺህ ስደተኞችን አንድ አገር በአጋጣሚ ስትቀበል የትኛዉም አገር ቢሆን ዝግጁ ላይሆን ይችላል።"
በሰብዓዊ ማዕቀፍ ዉስጥ ከወሲብ እና ስነተዋልዶ ጤና ጋር ተያይዞ የሚመጡ ቀዉሶች የሚፈጠሩት በጤና ጉዳዮች ብቻ አለመሆኑን ኃላፊው ይናገራሉ። ከፆታ ጋር ተያይዞ የሚመጡ ጥቃቶች ፣ ቀዉሶች በሚፈጠሩበት ጊዜ ይባባሳሉም ብለዋል።
ስደተኞች በጦርነት ፣ በተፈጥሮዊ ሃብቶች መንስኤ ወይም በሌሎች ቀዉሶች ምክንያት በከፍተኛ ቁጥር ሲሰደዱ የተቀባይ አገሮች አቅም እንደሚዳከም እንዲሁም የስደተኞች ማህበራዊ ልማዶች፣ ማለትም የርስ በርስ ግንኙነትና መረዳዳት እንደሚላላ ፋውስትን ያሆ ተናግረዋል። በእሳቸው ገለጻ በእንዲህ አይነት ሁኔታ ውስጥ ቀጥተኛ ተጠቂ የሚሆኑት ወጣት ልጃገረዶች እና ጎልማሳ ሴቶች ናቸው።
መርጋ ዮናስ
ሂሩት መለሰ