ምክትል ጠ/ሚ ኃይለ -ማርያም ደሳለኝና ኢህአዴግ፣
ዓርብ፣ ነሐሴ 18 2004የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ይሆናሉ ተብለው ለሚጠበቁት ለአቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ሥልጣን ለማስረከብ የሚካሄደው ፖለቲካዊ ዝግጅት ቀጥሏል ። የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ባራካ ኦባማ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝን ትናንት በስልክ አነጋግረዋቸዋል ። ኦባማ በዚሁ ወቅት አቶ ኃይለ ማርያም የኢትዮጵያ መንግሥት ለልማት ለዲሞክራሲ ና ለሰብአዊ መብቶች እንዲሁም ለአካባቢ አገራት ደህንነት የሚሰጠውን ድጋፍ እንዲያጠናክሩ ጠይቀዋል ። አቶ ኃይለ ማርያም ከዚህ ሌላ ትናንት አዲስ አበባ ተገኝተው በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሞት የተሰማቸውን ሃዘን የገለጹትን የሱዳንና የኬንያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ተቀብለው አነጋግረዋል ። የኢትዮጵያ መንግሥት ቃል አቀባይ አቶ በረከት ስምዖን ከ 3 አመት በኋላ በኢትዮጵያ ምርጫ እስከሚካሄድ ድረስ አቶ ኃይለ ማርያም የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ሥልጣን እንደሚይዙና የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሚያካሂደው አስቸኳይ ጉባኤ ፣ በይፋ ቃለ መሃላ እንደሚፈፅሙ ማስታወቃቸው ይታወሳል ። የቀድሞው የውሃ መሐንዲስ አቶ ኃይለ ማርያም የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነቱንና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትርነቱን ሥልጣን ከያዙ ገና 2 አመት አልሞላቸውም ። ከዚያ በፊት የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች መስተዳድር ፕሬዝዳንት ነበሩ ። የፈረንሳይ ዜና አገልግሎት እንደዘገበው አቶ ኃይለ ማርያም እምብዛም በፖለቲካው መስክ የሚታወቁ ሰው አይደሉም ። በሌላ በኩል በኢትዮጵያ በሞት ለተለዩት ለጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ብሔራዊው ሃዘን ዛሬም ቀጥሏል ። በብሔራዊ ቤተ መንግሥት በርካታ ሰዎች ሃዘናቸውን በመግለፅ ላይ ናቸው ።የኢትዮጵያ ጠ/ሚንስትር አቶ መለስ ዜናዊ ከዚህ ዓለም በሞት መለዬት፣ አገሪቱ ወደምን አቅጣጫ እንድታመራ ያደርግ ይሆን? የሚል ጥያቄ በሰፊው በማነጋገር ላይ ስለመሆኑ ይነገራል። በተለይ ምዕራባውያን አገሮች ፣ የአቶ መለስ ህልፈተ ህይወት፤ ከፍተኛ የሥልጣን ሽኩቻ ያመጣል ፣ ባካባቢውም መረጋጋት ላይኖር ይችላል የሚለውን ሥጋታቸውን ማንፀባራቀቸው አልታበለም። የኢህሰዴግ መንግሥት በበኩሉ ሥጋቱ መሠረት የለውም ይላል። ከለንደን ድልነሣ ጌታነህ ፤ ስለ ምክትል ጠ/ሚንስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የሚከተለውን ዘገባ አጠናቅሮ ልኮልናል።
ድልነሳ ጌታነህ
ተክሌ የኋላ
ነጋሽ መሐመድ