መፍትሔ የሚያስፈልገው ያለዕድሜ ጋብቻ
ረቡዕ፣ ጥቅምት 1 2010የብሪታንያውያኑ ግብረ ሰናዩ ድርጅት ሴቭ ዘ ችልድረን እና የዓለም ባንክ ዛሬ በዓለም አቀፍ ደረጃ ታስቦ የዋለውን የልጃገረዶች ቀንን ምክንያት በማድረግ በጋራ ያወጡት ጥናት እንደሚያሳየው፣ ንዑሱ የጋብቻ ዕድሜ በየሀገራቱ ሕገ መንግሥት ውስጥ ቢቀመጥም፣ ይኸው ሕግ እየተጣሰ በየቀኑ ካለዕድሜአቸው የመዳር እጣ የሚያጋጥማቸው ልጃገረዶች ቁጥር ከከ20,000 ይበልጣሉ። በአጠቃላይ ሕጉ ባለባቸው ሀገራት በያመቱ ወደ 7,5 ሚልዮን የሚጠጉ ልጃገረዶች እና ሕፃናት አለዕድሜአቸው ሲዳሩ፣ በሀገሮቻቸው ሕግ ከለላ የማይደረግላቸው ልጃገረዶች እና ሕፃናት ቁጥር 100 ሚልዮን ይደርሳል። እንደ ጥናቱ፣ ልጃገረዶች እና ሕፃናት ዕድሜአቸው ሳይደርስ የሚዳሩበት አሰራር በተለይ በማዕከላይ እና በምዕራብ አፍሪቃ ሃገራት ከፍተኛ ነው። በነዚሁ አካባቢዎች ብቻ በያመቱ 1,7 ሚልዮን ሕፃናት በጋብቻ ዕድሜ ላይ ያረፈው ገደብ እየተጣሰ ይዳራሉ። ይኸው ችግር በኢትዮጵያም እንደሚታይ እና በጤናም ላይ አሳሳቢ መዘዝ እንዳለው ለሴቶች እና ሕፃናት መብት የሚሟገቱት የሕግ ባለሙያ፣ የሴቶች ማረፊያ ልማት ማሕበር መስራችና ዳይሬክተር ወይዘሮ ማሪያ ሙኒር ገልጸዋል።
ሕፃናትን እና ልጃገረዶችን ከልጅነት ትዳር ለመጠበቅ የጋብቻን ዕድሜ ከፍ የሚያደርጉ ሕጎች ያወጡ ወይም የልጅነት ትዳርን በወላጅ ወይም በፍርድ ቤት ስምምነት የሚፈቅዱ ሕጎቻቸውን የሻሩ ሃገራት ቁጥር ካለፉት ጥቂት ጊዚያት ከፍ እያለ መምጣቱን ጥናቱን ያወጡት ድርጅቶች አመልክተዋል። ይሁን እንጂ፣ ዝቅተኛ ተብሎ የተደነገገ የጋብቻ ዕድሜ ገደብን በሕገ መንግሥታቸው ያስቀመጡት ሃገራት ሕጉን በተግባር መተርጎሙ ዛሬም ትልቅ ተግዳሮት እንደሆነባቸው ነው የሚናገሩት። ይህ ችግር ሕጉ ላለባት ኢትዮጵያም አዲስ እንዳልሆነ ለሴቶች እና ሕፃናት መብት የሚሟገቱት የሕግ ባለሙያ፣ የሴቶች ማረፊያ ልማት ማህበር መስራችና ዳይሬክተር ወይዘሮ ማሪያ ሙኒር ያረጋግጣሉ።
እንደ ወይዘሮ ማሪያ አስተሳሰብ፣ ችግሩን ለማስወገድ ከሕጉ ጎን ለጎን ብዙ መሰራት ይኖርበታል። የልጅነት ጋብቻ እስካልጠፋ ድረስ ወንዶች እና ሴቶች በሁሉም የኑሮ ዘርፎች እኩል እድል የሚያገኙበት ዓለም እንደማይኖር ጥናቱን ከዓለም ባንክ ጋር በጋራ ያዘጋጀው የሴቭ ዘ ችልድረን ኃላፊ ሄለ ቶርኒንግ ሽሚት ገልጸው ሕግ ማውጣቱ የመጀመሪያ ዋና ርምጃ ቢሆንም ፣ ይህንን ጎጂ አሰራር ለማጥፋት ቀጣይ ጥረት ያስፈልጋል ብለዋል። በዚህም መሰረት፣ የሕፃናት ጋብቻ በተለይ በማዕከላይ እና በምዕራብ አፍሪቃ ሃገራት የደቀነውን ችግር የሚያጎላ እና ይህንኑ አሰራር ማብቃት ስለሚቻልበት ጉዳይ የሚመክር ጉባዔ ከአስራ ሁለት ቀናት በኋላ፣ እአአ ከጥቅምት 23 እስከ 25፣ 2017 ዓም በሴኔጋል መዲና ዳካር ይካሄዳል።
አርያም ተክሌ
ሸዋዬ ለገሠ